The Federal Supreme Court of Ethiopia


Channel's geo and language: not specified, not specified
Category: not specified


Federal Supreme Court is the highest court in Ethiopia. It is constitutionaly established court. It is also one of the three pillars of the federal state that assures the check and balance in & among.

Related channels  |  Similar channels

Channel's geo and language
not specified, not specified
Category
not specified
Statistics
Posts filter


Reform Update OCJ (Issue 1, no 1).pdf
4.5Mb
የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ጽ/ቤት ወቅታዊ የለውጥ ሂደት መረጃ (REFORM UPDATE) አዘጋጅቶ በኤሌክትሮኒክ መልዕክት አሰራጭቷል፡፡
እንድታነቡት ጋብዘናችኋል፡፡


የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዝደንት ክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የ2012 ዓ.ም የዳኝነት የስራ ዓመት መገባደድ እና የ2013 አዲስ ዓመት መባቻን አስመልክቶ ለዳኞች የምስጋና መግለጫ ልከዋል፡፡ የመግለጫው ሙሉ ይዘት እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

ክቡራንና ክቡራት ዳኞች

ባሳለፍነው የዳኝነት ዘመን በፍርድ ቤቶች ለተስተዋለው የአገልግሎት አሰጣጥ መሻሻል ያሳያነው የዳኝነት ኃላፊነት ስሜት፤ የሙያ ስነምግባርና ክብር የሚመሰገን ነው፡፡ ለተገኘው ውጤትም በፍርድ ቤቱ ከፍተኛ አመራር አካላት በኩል ለተፈጠረው የጋራ ራዕይ፣ ግልጽነት፣ የመተማመን መንፈስ እና የስራ ትጋር ያለኝን አድናቆት እገልጻለሁ!!

የዳኝነት ዘርፉን በተሟላ ቅርጽና ይዘት የማሻሻል አቅም የሚፈጥሩና የማዕዘን ድንጋይ ተደርገው ሊወሰዱ የሚችሉ የፌዴራሉ መንግስት የዳኝነት አካል ራሱን በሙሉ ነጻነት ማስተዳደር የሚያስችል እና የፍርድ ቤቶችን አደረጃጀትና ስልጣን የሚወስነውን አዋጅ በአዲስ መልክ የሚያሻሽል ረቂቅ አዋጆች ተዘጋጅተው ለምክር ቤቱ ቀርበዋል፡፡ ምክር ቤቱም ላቀረባቸው የማብራሪያ ጥያቄዎች ዝረዝር ማብራሪያ በመስጠት በኮቪድ ምክንያት በሙሉ ዓቅሙ ስራ እንዳይሰራ ከማድረጉ በፊት የመጽደቅ የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ ማድረስ ተችሏል፡፡

ሌላው በዚህ ዓመት ከተከናወኑት ዓበይት ስራዎች መካከል በዓለማችን እንዲሁም በሃገራችን በተከሰተውና እስከአሁንም መፍትሄ ባልተገኘለት የኮቪድ 19 ወርሽኝ ምክንያት የዜጎችን የዳኝነት መብት እና በጤና በህይወት የመኖር መብት በአንድ ላይ ለማረጋገጥ ከገባንበት አጣብቂኝ ውስጥ ለመውጣት የሰራነው ስራ አንዱ ነው፡፡

ፍርድ ቤቶቻችን የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ማሰራጫ ማዕከል እንዳይሆኑ ለማድረግ በተወሰደው አስተዳደራዊ እርምጃ ፍ/ቤቶች ከመጋቢት እስከ ሐምሌ አጋማሽ በከፊል ዝግ እንዲሆኑ ተደርገዋል፡፡ በዚሀም ምክንያት ወደ ፍርድ ቤቶቻችን ሊመጣ የሚችል የመዛግብት ፍሰት የቀነሰ ቢሆንም ዳኞች በቤታችሁና በቢሯችሁ ለምርመራ ለደረሱ መዛግብት እልባት ለመስጠት ጊዜያችሁን በመጠቀማችሁ በፌዴራል ፍ/ቤቶች ደረጃ 140 ሺህ ለሚሆኑ መዛግበት እልባት መስጠት ተችሏል፡፡

በወረርሽኙ ምክንያት ፍ/ቤቶቸ በከፊል ዝግ ሆነው እንዲቆዩ በተደረጉበት ተመሳሳይ ጊዜ አስቸኳይነት ያላቸውን ጉዳዮች በተረኛ ችሎት በማስተናገድ ለ7 ሺህ መዛግብት እልባት ተሰጥቷል፡፡ ይህም በአጣዳፊ ሁኔታ ዳኝነት ለሚሹ ወገኖቻችን ከራሳችሁ ደህንነት ይልቅ የእነርሱን በማስቀደም አወንታዊ ምላሽ ለመስጠት ያገኛችሁትን እድል በአግባቡ የተጠቀማችሁበት ለመሆኑ ያሳያችሁበት ነው ለማለት ያስችላል፡፡

የዳኝነት የስራ ጫና ለመቀነስ ከ150 በላይ የረዳት ዳኞች ቅጥር በማከናወን የዳኞችን የስራ ሸክም ለማቃለልም ተችሏል፡፡ የሬጂስትራር ባለሙያዎቸን በበቂ ቁጥር በመሾምና የሙያ ብቃታቸውን የሚያጎለብት ስልጠና ተሰጥቷል፤ የአሰራር ለውጥ ተደርጓል፡፡ ከተገልጋዮቻችን ያገኘነው ግብረመልስ የሬጂስትራር አገልግሎት አሰጣጥ ቅልጥፍናም መጨመሩን ጠቁሞናል፡፡
የተወደዳችሁ ዳኞች

የዳኝነት አንዱ መገለጫ ባህሪው ግልጽነት ነው፡፡ ዳኝነትን በግልጽ ችሎት ለመስጠት የማያስችሉ፤ ለዳኞችና ለተገልጋይ ምቾት የሌላቸውን ምድብ ችሎቶችን በመለየት የተሻለ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ ህንጻዎችን በመከራየት ችግሩን ለመፍታት የተደረገው ጥረትም አበረታች ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ከመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት የመናገሻ እና የአራዳ ምድብ ችሎቶች እንዲሁም ከከፍተኛ ፍ/ቤት ጦሃይሎች ምድብ ችሎት ለአብነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

እንደምትገነዘቡት የዳኝነት ነጻነትን ከማስጠበቅ አንጻር ያስመዘገብንባቸው አኩሪ እና ፈር ቀዳጅ ውጤቶችም አሉ፡፡ የዳኝነት አካሉን የበጀት ነጻነት ለማስጠበቅ በተሰራው ስራ በህገመንግስቱ በተቀመጠው ድንጋጌ መሰረት የፍርድ ቤትን በጀት ለመጀመሪያ ጊዜ በቀጥታ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱ በማቅረብ በገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ምኒስቴር ከተቀመጠው የበጀት ጣሪያ በላይ በማስፈቀድ በጀቱን በውጤታማነት ጥቅም ላይ ማዋል ተችሏል፡፡

ከዚህ ጎን ለጎን የዳኞችን ግለሰባዊ ነጻነትና መብት አስከብሮ ገለልተኛ የዳኝነት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታችን ለመፍጠር በተደረጉ ጥረቶች ዳኞች ያለባቸው የስራ ሃላፊነትና ጫና እነዲሁም የሃገሪቱን ኢኮኖሚ ከግንዛቤ ያስገባ የደመወዝ ማስተካከያም መደረጉ ይታወቃል፡፡ በእቅድ ከተያዘለት ጊዜ በላይ የወሰደው የዳኞች የጋራ መኖሪያ ሕንጻ ግንባታ እንዲጠናቀቅ ከመንግስትና ከተቋራጩ ድርጅት ጋር በተደረጉ ያልተቋረጠ ክትትልና የአስተዳደር ድጋፍ ስራችን ፍሬ አፍርቶ ግንባታውን ለማጠናቀቅ ችለናል፡፡ ዳኞች በቤት ኪራይ ሲደርስባቸው ከነበረው እንግልት የሚያወጣቸውና መኖሪያ ብቻ ሳይሆን እንደቢሮም የሚገለገሉባቸው 140 ባለ ሶስት እና 138 ባለ ሁለት መኝታ ክፍል ቤቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ዝግጁ ሆነዋል፡፡

ከላይ የጠቀስናቸው አመርቂ ውጤቶች ቢኖሩም አሁንም ያልተሸገርናቸውና ጉዳዮች አሉ፡፡ በጀመርነው አዲስ የዳኝነት ዓመት (2013 ዓ.ም) የጉዳዮች ፍሰት አስተዳደር ስርዓታችን እንዱ በልዩ ትኩረት ልንሰራበት የሚገባ ዘርፍ ነው፡፡ በጀምር ላይ ያለውና የመደበኛ ፍርድ ቤቶቻችንን ጫና ለመቀነስ የሚያስችል ፍርድ ቤት መር የአስማሚነት አገልግሎት ተጠናክሮ የሚቀጥልበት ሁኔታን ማመቻቸት ያስፈልገናል፡፡

የምንሰጠው ዳኝነት ከቅልጥፍና አንጻር መልካም ደረጃ ላይ ደርሷል ሊባል የሚችል ቢሆንም ከምንሰጠው ዳኝነት ጥራት አኳያ ውስንነቶች እንዳሉ በተለያየ መንገድ የሚደርሱን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የዳኝነት ነጻነት ሚዛን መጠበቂያ የሆነው የዳኝነት ተጠያቂነት ስርዓታችንንም እንደዚሁ የምንፈትሽና በረቂቅ ደረጃ የተዘጋጀን የዲሲፕሊንና ስነምግባር መመሪያ እንዲሁም የአፈጻጸም ምዘና መመሪያን በማጽደቅ ስራ ላይ የምናውል ይሆናል፡፡

ፍርድ ቤቶቻችን ለአራት ወራት በከፊል ዝግ ሆነው በመቆቀታቸው በወቅቱ ሊታዩ የሚገባቸው ጉዳዮች ሳይታዩና መዝገብ ሳይከፈትላቸው በመቆየታቸው በጀመርነው አዲስ አመት የመዝገብ ፍሰቱ መጨመሩ የማይቀር ነው፡፡ ለዚህም በተባበረ መንፈስ ጠንክረን በመስራት በፍርድ ቤቶቻችን እየታየ ያለውን ለውጥ በማስቀጠል አምና ያገኘነውን የሚያስመሰግን ውጤት ከፍ ባለ ደረጃ እንድንደግመው በጋራ ራዕያችን ላይ በጽናት እንድንቆም በዚሁ አጋጣሚ ልጠይቃችሁ አፈልጋለሁ፡፡

የአዲሱ አመት የመጀመሪያው ወር የእረፍት ጊዜያችሁ አንዲሆን መወሰኑ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በፍርድ ቤቶቻችን የተለመደ አሰራር አብዛኛዎቻችሁ ውዝፍ መዛግብትን በማጥራት ስራ ላይ በፈቃዳችሁ የምትቆዩ መሆናችሁ የሚያስመሰግናችሁ ነው፡፡

ወድ ዳኞች በመጨረሻም

መጪው አዲስ ዘመን ቃል የገባንለት ህጋዊና ፍትሃዊ ዳኝነት የመስጠት ተልዕኳችንን በእውቀትና በሙያ፤ በገለልተኝነትና በሐቀኝት፤ በቅልጥፍናና በጥራት፤ በነጻነትና በተጠያቂነት የምንወጣበት፤ ህብረተሰቡ በፍርድ ቤቶቻችን ላይ ያለው ዓመኔታ ከፍ የሚልበት እና ለሌላ ተጨማሪ ስኬት የምንበቃበት ዘመን እንዲሆንልን እመኛለሁ!!

ክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ መንግስቱ
የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዝደንት
ጷጉሜ 3 ቀን 2012 ዓ.ም


የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉባዔ 5ኛ ዓመታዊ ጉባዔ
የአቋም መግለጫ
ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉባዔ በፌዴራል ፍ/ቤቶች አዋጅ 25/88 ከአንቀጽ 31-34 በተደነገገው መሰረት የተቋቋመና በዳኝነት ሥራ አስተዳደር ረገድ በሚያጋጥሙ ችግሮች ላይ ተወያይቶ መፍትሔ የመስጠት፤ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የዳኝነት አሰራርን ለማሻሻል የሚረዱ መመሪያዎችና ውሳኔዎችን የማሳለፍ፤ አዳዲስ ሕጎች እንዲወጡ ወይም ነባር ሕጎች እንዲሻሻሉ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሃሰብ የማቅረብ፤ የዳኝነት ስራ አካሄድን ለማቀላጠፍና ለማጠናከር የሚረዱ ሌሎች ተግባራትን የማከናውን እና ለጉባዔው ስራ አፈጻጸም አስፈላጊውን ደንብ የማውጣት ስልጣንና ተግባር የተሰጠው ጉባዔ ነው፡፡ በዚህም መሰረት የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉባዔ 5ኛውን ዓመታዊ ጉባዔ ዛሬ ነሐሴ 30 ቀን 2012 ዓ.ም በፌዴራልና በክልል ፍርድ ቤቶች ተቋማዊና ዳኝነታዊ ነጻነት ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ውይይት አካሂዷል፡፡
https://www.facebook.com/permalink.php?story_fbid=1880757975407599&id=265784033571676&__xts__[0]=68.ARCabbnoLWxFtzychQ5SskiDyKaZ8e93KdpE8piSfHJs1zM7RRnjM3VtctUAh-cOiDcFHFFBPs85E7ywAYHHErivyBg6Z8ErQjPqG_htoCzGmnAvyxjvMtm_Thn1QEHuVjFe-ue5VuO9JbRit00q3AdqFQrxW9cLk-s2OuxtjHqVPwj7UgsgZKrBPSn5ebxgkSiUtZjO4IeVfn0uN407znLT2r_FBGaXS8Tp5_Z8LLpP3qoVY3dLM6vEETJOa38L2fOz2F83AngsFnC2GOdC0CVY9KBq2UBW8obeivxHp-mxRKYZFmQwiuQb_xWwyd62N4aWx19fN2_g1fABLGZDpZMm-w&__tn__=-R


5ኛው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉባዔ


የፍ/ቤቱን ሴት ሰራተኞች ማብቃትና ሃላፊነታቸዉን በብቃት መወጣት የሚያስችሉ ድጋፎችን ማመቻቸት እንዲሁም ምቹ የስራ አካባቢ መፍጠር አስፈላጊነት ተጠቆመ፡፡

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የፍ/ቤቱን ሴቶች ባለሙያዎች ማብቃትና ኃላፊነታቸዉን በከፍተኛ ብቃት እንዲወጡ የሚያስችል አሰራሮችን ለማመቻቸት ከሴት ዳይሬክተሮች፣ የቡድን መሪዎች፣ ከፍተኛ ባለሙያዎች እና የፅዳት ሰራተኛ ተወካዬች ጋር ነሐሴ 28 ቀን 2012 ዓ.ም ዉይይት አድርገዋል፡፡

በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በተለያዩ የስራ ዘርፎች ላይ የሚገኙ ሴት ባለሙያዎችን አቅም በማጠናከርና ምቹ የስራ ቦታ በመፍጠር ፍርድ ቤቱን የተሻለ አገልግሎት ሰጪ ተቋም በማድረግ በተገልጋይ ዘንድ መልካም ገፅታ ለመፍጠር በጋራ መስራት ይገባል ያሉት ክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ ውይይቱ ያሉንን ሃብቶች በአግባቡ በመጠበቅና በመጠቀም ለቀጣጥ ትዉልድ የሚተርፍ ስራ ለመስራት በአስተሳሰብ የተቀየረ ማህበረሰብ በፍርድ ቤታችን የመፍጠር ዓላማ ያነገበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
https://www.facebook.com/permalink.php?story_fbid=1878900975593299&id=265784033571676


“በፍ/ቤት ማሻሻያ ስራዎች ትኩረት ከሚሰጥባቸው ስራዎች መካከል አንዱ የዳኞችን ዓቅም በዕውቀትና በክህሎት ማሳደግ ነው” ሲሉ የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ፕሬዝደንት ክብርት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ ገለጹ፡፡

ክብርት ፕሬዝደንቷ ይህን የገለጹት የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከፌዴራል ዳኞች አስተዳደር ጉባዔ ጽ/ቤት ጋር በመተባበር ያዘጋጀውን የስድስት ቀን ስልጠና መርሃ ግብር ለመክፈት ባደረጉት ንግግር ነው፡፡

ዳኞች በየጊዜው በህግ አውጪው አካል የሚወጡ አዲስ ህጎችን ወይም ማሻሻያዎችን ተረድተው የመተርጎም መሰረታዊ ክህሎት አላቸው ያሉት ክብርት ፕሬዝደንቷ፤ አንዳንድ ህጎች ዓለም ዓቀፍ እንድምታ ያላቸው እና እያደጉ የሚሄዱ የህብረተሰቡን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መስተጋብሮችን የሚነኩ በመሆኑ በህጎቹ ዙሪያ መነጋገር እና ሃሳብን ማዳበር አስፈላጊ መሆኑን በንግግራቸው ገልጸዋል፡፡

ነሐሴ 25 ቀን 2012 ዓ.ም የጀመረው የስልጠና መርሃ-ግብር የኢፌዲሪ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እየተጠናቀቀ ባለው ዓመት ካወጣቸው ህጎች መካከል የተሻሻለው የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር የወጣ አዋጅ ቁጥር 1176/2012፤ የፌዴራል የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 1183/2012፤ የጥላቻ ንግግርን እና የሐሰተኛ መረጃ ስርጨትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣ አዋጅ ቁጥር 1185/2012 እና ምክር ቤቱ ዓለምአቀፍ ስምምነቶችን በማጽደቅ ስልጣኑ መሰረት የግልግል ዳኝነት ውሳኔዎች እውቅና የመስጠት እና የመፈጸም ስምምነት (New York Convention) ማጽደቂያ አዋጅ ቁጥር 1184/2012 ላይ ያተኮረ ነው፡፡

ስልጠናው ዳኞች በአዋጆቹ ላይ ወሰረታዊና ወጥ የሆነ ግንዛቤን በመጨበጥ ለዳኝነት በሚቀርቡላቸው ተመሳሳይና ተቀራራቢ ጉዳዮች ላይ ተገማች ዳኝነት መስጠት የሚያስችላቸውን አቅም መፍጠር ዓላማ ያደረገ ነው ተብሏል፡፡

በስልጠናው መጀመሪያ ቀን የጥላቻ ንግግርን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣ ዓዋጅን በማርቀቅና ግብአት በመስጠት ሂደት ተሳትፎ ያደረጉት አቶ ሰለሞን ጎሹ የዓዋጁን ዓላማ፣ አስፈላጊነት፤ አመክንዮ እና በማርቀቅ ሂደት በተካሄዱ የውይይት መድረኮች የተሳታዎችን ግብረመልስ ይዘት አብራርተዋል፡፡

የስልጠናው ዘዴ የአዋጁን ይዘትና መነሻ ሃሳብን በገለጻ እንዲሁም በመወያያ ጥያቄዎች ላይ የቡድን የሃሳብ ልውውጥ ማካሄድ ሲሆን በየስልጠና ርዕሱ የሚሳተፉ ዳኞች ተዛማጅ ጉዳዮችን በሚያዩ ችሎቶች ተመድበው የሚሰሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡

በስድስቱ ቀን ስልጠና በአጠቃላይ 200 የሚሆኑ ዳኞች እንደሚሳተፉ ስልጠናውን ከሚያስተባብረው ከፌዴራል ዳኞች አስተዳደር ጉባዔ ጽ/ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡

የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

https://www.facebook.com/permalink.php?story_fbid=1877631252386938&id=265784033571676&__cft__[0]=AZVdWMRYXCiO4-on4oA0lrgvhzrcTbq6lpnVdZIixgrfdJVVFCfubQe4fh5bjVoP72SEXQprlAQeziN4urmQ6I52lb1g-kiCvYPKNClpWBANO6G0jR3r-yo7DJPjel4yus5JsNoKGqLYTlAhPf0ZnP-StxLJ7P8Z3pVOEmFKEZHcxQ&__tn__=%2CP-R


የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በ2012 በጀት ዓመት ለ15 ሺህ 563 መዛግብት እልባት ሰጠ

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በ2012 በጀት ዓመት ለ19 ሺህ 981 መዛግብት እልባት ለመስጠት ከያዘው ዕቅድ ውስጥ ለ15 ሺህ 563 መዛግብት እልባት የሰጠ ሲሆን ይህም በበጀት ዓመቱ ከቀረቡለት 18 ሺህ 928 መዛግብት አንጻር አፈጻጸሙ 82.22 በመቶ መሆኑን ያሳያል፡፡

የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከፍተኛ አመራሮችና ዳኞች በዳኝነት ዘርፉ የ2012 ዕቅድ አፈጻጸም ላይ ነሐሴ 2 ቀን 2012 ዓ.ም በፍርድ ቤቱ የስብሰባ አዳራሽ ባካሄዱት የጋራ ውይይት የመዝገብ አፈጻጸሙ ፍርድ ቤቱ በኮረና ቫይረስ ወረርሽኝ ምክንያት በከፊል ዝግ ሆኖ በቆየበት ጊዜ ጭምር የተመዘገበ በመሆኑ አበረታች ውጤት የታየበት እንደነበር ተሳታፊዎቹ ገልጸዋል፡፡

በበጀት ዓመቱ በፍርድ ቤቱ ዕልባት እንዲያገኙ በዕቅድ ከተያዙት መዛግብት መካከል ከሐምሌ 2011 ዓ.ም እስከ መጋቢት 2012 ዓ.ም መጀመሪያ ማለትም የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የኮረና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል በከፊል ዝግ ሆነው እንዲቆዩ እስከተወሰነበት ጊዜ ድረስ ዕልባት ማግኘት ከሚገባቸው 13,987 መዛግብት ውስጥ 12,085 መዛግብት ዕልባት በማግኘታቸው በተጠቀሰው ጊዜ ፍርድ ቤቱ የዕቅዱን 86.4% መፈጸም እንደቻለ በቀረበው ሪፖርት ተጠቅሷል፡፡

ፍ/ቤቱ ከመጋቢት 2012 ዓ.ም መጀመሪያ ሳምንት በኋላ በከፊል ዝግ ሆኖ እንዲቆይ መወሰኑን ተከትሎ እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ ድረስ በቀጠሮ ላይ ከሚገኙ እንዲሁም አዲሰ እና እንደገና ከተከፈቱ 6 ሺህ 840 መዛግብት መካከል ለ3 ሺህ 478 መዘግብት እልባት መሰጠቱም ተነግሯል፡፡

እልባት ከተሰጣቸው 15 ሺህ 563 መዛግብት መካከል 14 ሺህ 780 ጉዳዮች ወይም 95 በመቶ ያህሉ ከአንድ ወር እስከ አንድ ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ውሳኔ ያገኙ ናቸው፡፡

በሪፖርቱ ላይ በተደረው ውይይት ከመዛግብት አፈጻጸም በተጨማሪ ፍርድ ቤቱ በዕቅድ ባስቀመጣቸው ግቦች ላይ በተለይም የዳኝነት ነጻነት፣ ገለልተኝነትና ተጠያቂነት መርሆች አፈጻጸምን ለማሻሻል፣ የዳኝነት ጥራትን ለማሳደግ፣ የዳኝነት አገልግሎት ቅልጥፍናን ለማጎልበት እንዲሁም የዳኝነት አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል በተሰሩ ስራዎች ላይ በሰፊው ውይይት ተካሂዷል፡፡

የሶስቱ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የሆኑት የፌዴራል ጠቅላይ፣ ከፍተኛ እና መጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤቶች በ2012 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸማቸው ላይ ነሐሴ 21 ቀን 2012 ዓ.ም የጋራ ውይይት በማድረግ በቀጣይ ስራዎች ላይ አቅጣጫ እንዲሚያስቀምጡ ታውቋል፡፡

የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት


በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በሬጂስትራር ጽ/ቤት ከነሐሴ 1 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ አዲስ መዝገብ ለመክፈት የወጣ መርሃ-ግብር
የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም ፍ/ቤቱ በወጣው መመሪያ መሰረት አዲስ ፋይሎች የመክፈት አገልግሎት ከነሐሴ 1 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ መስጠት የሚጀምር መሆኑ ተገልጿል፡፡ በዚህም ምክንያት ባለጉዳዮች በተመሳሳይ ቀን ወደ ፍ/ቤቱ በብዛት በመምጣት መጨናነቅ እንዳይፈጠርና ተገልጋዩ የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ለመከላከል ሊወሰድ የሚገባውን አካላዊ ርቀት መጠበቅ እንዲችል ከአዲስ አበባም ሆነ ከክልል የሚመጡ ባለጉዳዮች የሚስተናገዱበት መርሃ ግብር አውጥቷል፡፡ የፍርድ ቤቱ ሬጂስትራር ጽ/ቤትም ተገልጋዮች ከዚህ በታች በተዘጋጀው መርሃ ግብር መሰረት በመምጣት አገልግሎቱን ማገኘት የሚችሉ መሆኑን አስታውቋል፡፡
1. የሰበር አጣሪ ባለጉዳዮች
1.1. የመጨረሻ ውሳኔ ከታህሳስ 10- ጥር 30 ቀን 2012 ዓ.ም የተሰጠባቸው መዝገቦች ከነሐሴ 1 - 8 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
1.2. የመጨረሻ ውሳኔ ከየካቲት 1- 30 ቀን 2012 ዓ.ም የተሰጠባቸው መዝገቦች ከነሐሴ 11- 15 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
1.3. የመጨረሻ ውሳኔ ከመጋቢት 1 - ሚያዚያ 30 ቀን 2012 ዓ.ም የተሰጠባቸው መዝገቦች ከነሐሴ 18 - 22 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
1.4. በመረጃ እጥረት ምክንያት በፕሮግራሙ መሰረት ቀርበው ያልተስተናገዱ ባለጉዳዮች ካሉ ከነሓሴ 25 - 29 ቀን 2012 ዓ.ም ይስተናገዳሉ፡፡
2. የወንጀል ይግባኝ ባይ ባለጉዳዮች
2.1. ከየካቲት 10 እስከ መጋቢት 30 ቀን 2012 ዓ.ም የውሳኔ ግልባጭ የደረሳቸው ባለጉዳዮች ከነሐሴ 1- 8 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
2.2. ከሚያዚያ 1 እስከ ግንቦት 30 ቀን 2012 ዓ.ም የውሳኔ ግልባጭ የደረሳቸው ባለጉዳዮች ከነሐሴ 11- 15 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
2.3. ከሰኔ 1 እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2012 ዓ.ም የውሳኔ ግልባጭ የደረሳቸው ባለጉዳዮች ከነሐሴ 18 – 22 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
2.4. በመረጃ እጥረት ምክንያት በፕሮግራሙ መሰረት ቀርበው ያልተስተናገዱ ባለጉዳዮች ካሉ ከነሓሴ 25 - 29 ቀን 2012 ዓ.ም ይስተናገዳሉ፡፡
3. የፍትሐብሔር ይግባኝ ባለጉዳዮች
3.1. ከጥር 10 እስከ የካቲት 30 ቀን 2012 ዓ.ም የውሳኔ ግልባጭ የደረሳቸው ባለጉዳዮች ከነሐሴ 1- 8 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
3.2. ከመጋቢት 1 እስከ ሚያዚያ 30 ቀን 2012 ዓ.ም የውሳኔ ግልባጭ የደረሳቸው ባለጉዳዮች ከነሐሴ 11- 15 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
3.3. ከግንቦት 1 እስከ ግንቦት 30 ቀን 2012 ዓ.ም የውሳኔ ግልባጭ የደረሳቸው ባለጉዳዮች ከነሐሴ 18 – 22 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
3.4. በመረጃ እጥረት ምክንያት በፕሮግራሙ መሰረት ቀርበው ያልተስተናገዱ ባለጉዳዮች ካሉ ከነሓሴ 25 - 29 ቀን 2012 ዓ.ም ይስተናገዳሉ፡፡
4. በኢ- ፋይሊንግ ጉዳያቸውን ለሚያቀርቡ ባለጉዳዮች
ከላይ ለሰበር አጣሪ፣ ለወንጀል እና ለፍትሐብሔት ይግባኝ ባለጉዳዮች በወጣ ው መርሃ-ግብር መሰረት በክልሎች በሚገኙ ተወካዮቻችን በኩል የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
ማሳሰቢያ
• የወንጀል ይግባኝ መርሃ ግብር ታሳቢ ያደረገው ይግባኝ ባዮች የውሳኔ ግልባጭ ጠይቀው መሸኛ የተሰጠበትን ቀን ነው፡፡
• አስቸኳይነት ያላቸው ጉዳዮች ተብለው በመመሪያው የተለዩ ጉዳዮች ከሓምሌ 13 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ እየተስተናገዱ ይገኛሉ፡፡
• የሰበር፤ የወንጀል እና የፍትሐብሔት ይግባን ማቅረቢያ ጊዜ ያለፈባቸው ባለጉዳዮች ያለፕሮግራም ከ ሐምሌ 11 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ እየተስተናገዱ ይገኛሉ፡፡
• ፋይል ለማስከፈት የሚቀርቡ ባለጉዳዮች የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል (ማስክ) መጠቀም ግዴታ ነው፡፡ እንዲሁም ፍ/ቤቱ ባዘጋጀው በንጽህና መጠበቂያ ውሃና ሳሙና እጃቸውን መታጠብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ በመግቢያ በር አካባቢ ባሉ ባለሙያዎች ሙቀታቸውን ተለክተው ወደ ግቢው እንዲገቡ ይገደዳሉ፡፡
የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሬጂስትራር ጽ/ቤት


ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ባለጉዳዮች በሙሉ

የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሐምሌ 10/2012 ዓ.ም ባወጣው የስራ መመሪያ መሰረት በአዲስ አበባ ከሚገኙ ባለጉዳዮች የሚቀርቡ የሰበር አቤቱታዎችን ከሐምሌ 13/2012 ዓ.ም ጀምሮ ማስተናገድ ይጀምራል፡፡ ነገር ግን የባለጉዳዮችን ፍሰት ለመቀነስና የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል ሊወሰድ ከሚገቡ የጥንቃቄ እርምጃዎች መካከል አካላዊ ርቀትን መተግበር ያስችል ዘንድ የሬጅስትራር ፅህፈት ቤት የፍርድ ቤቱን ባለጉዳዮች የሚያስተናግድበትን መርሃ ግብር አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ መሰረት፡-

1. የመጨረሻ ውሳኔ ከታህሳስ 10/2012 ዓ.ም እስከ ጥር 20/2012 ዓ.ም የተሰጠባቸው መዝገቦች ከሐምሌ 13 እስከ ሐምሌ 17/2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡

2. የመጨረሻ ውሳኔ ከጥር 21 እስከ የካቲት 30/2012 ዓ.ም የተሰጠባቸው መዝገቦች ከሐምሌ 20 እስከ ሐምሌ 24/2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡

3. የመጨረሻ ውሳኔ ከመጋቢት 1 እስከ ሚያዝያ 13 የተሰጠባቸው መዝገቦች ከሐምሌ 27 እስከ ነሐሴ 1/2012 ዓ.ም ድረስ ቀርበው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡

ማሳሰቢያ፡-

 አስቸኳይ ተብለው የተለዩ ጉዳዮች ያለ ኘሮግራም የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
 ከአዲስ አበባ ውጪ ላሉ ባለጉዳዮች ከነሐሴ 1/2012 ዓ.ም ጀምሮ በሚወጣው ኘሮግራም መሰረት የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
 የአዲስ አባባ ባለጉዳዮች ለሰበር አቤቱታ ማቅረብ የሚችሉት በፌዴራልና አዲስ አበባ ከተማ ፍርድ ቤት እና አስተዳደር መስሪያ ቤት የተሰጡ ውሳኔዎችን የሚመለከት ነው፡፡
 ዘጠና ቀን ሰበር ማቅረቢያ ያላለፈባቸው ባለጉዳዮች ያለኘሮግራም የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
 ፋይል ለመክፈት የሚቀርቡ ባለጉዳዮች የአፍ መሸፈኛ ማክስ እና ፍርድ ቤቱ በሚያዘጋጀው የንፅህና መጠበቂያ ቦታ መታጠብ፤ ሙቀታቸውን መለካት ይጠበቅባቸዋል፡፡

ዋና ሬጂስትራር


news release.pdf
1.7Mb
በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከሀምሌ 13/2012 ዓ.ም ጀምሮ ስለሚሰጡ ተጨማሪ የዳኝነት አገልግሎቶች የተሰጠ መግለጫ


2. በነሀሴ ወር 2012 ዓ.ም የሚሰጡ አገልግሎቶች
 በሁሉም ደረጃ ባሉት ፍ/ቤቶች አዲስ መዝገቦችን ማለትም ቀጥታ ክስ፣ ይግባኝ እና አፈፃፀም መዝገቦችን የመክፈት አገልግሎት ይጀመራል፡፡
 ዳኞች በየዓመቱ በነሐሴ ወር እረፍት የሚወስዱ የነበረ ቢሆንም ወደፊት በዳኝነት ስራ ላይ የሚፈጠረውን የስራ ጫና ለማቃለል እንዲረዳ ዳኞች በስራ ገበታቸው በመገኘት አዲስ የሚከፈቱ መዝገቦችን በመመርመር በጉዳዮች ፍሰት አስተዳደር መርህ መሰረት ቀጠሮ ወይም ተገቢውን ትእዛዝ የሚሰጡ ይሆናል፡፡
 አስቸኳይነት ያላቸው ጉዳዮች ማለትም ቀደም ሲል በተረኛ ችሎት ሲስተናገዱ የነበሩ ጉዳዮች በተረኛ ችሎት መስተናገዳቸውን ይቀጥላሉ፡፡
 የምርመራ መዛግብት የማጥራት ስራ በተጨማሪነት የሚከናወን ይሆናል፡፡
3. በመስከረም ወር 2013 ዓ.ም የሚሰጡ አገልግሎቶች
 የመስከረም ወር 2013ዓ.ም የዳኞች የእረፍት ጊዜ ይሆናል፡፡
 አስቸኳይ ጉዳዮች ማለትም በተረኛ ችሎት ሲስተናገዱ የነበሩ ጉዳዮች እስከ መስከረም 30/2013ዓ.ም በተረኛ ችሎት የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
ፍርድ ቤቶች አብዛኛውን አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን ተከትሎ የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ለመከላከል በሁሉም ፍርድ ቤቶች በአስገዳጅነት ሊተገበሩ የሚገባቸዉ የጥንቃቄ እርምጃዎች
1. በቀጣይ የሚሰጡ አገልግሎቶች ቢያንስ ሁለት ሜትር ርቀትን በጠበቀ ሁኔታ እንዲከናወን ማድረግ፤
2. ሰራተኞችም ይሁኑ ተገልጋዮች የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ እንዲጠቀሙ ማድረግ፤
3. ለፍ/ቤቱ ማህበረሰብና ለተገልጋይ የሚያገለግሉ የንፅህና መጠበቂያ ግብአቶችን እንደ የእጅ ንፅህና መጠበቂያ ውሃ፣ ሳሙና፣ አልኮል እና ሳኒታይዘር የመሳሰሉትን ማሟላትና እንዲጠቀም ማድረግ፡፡
4. ተገልጋይም ሆነ የፍ/ቤቱ ማህበረሰብ ወደ ግቢ ከመግባቱ በፊት የሙቀት መጠን እንዲለካ ማድረግና የሙቀት መጠኑ ከ38 ዲግሪ በላይ ከሆነ ተለይቶ ማቆየት እና በአቅራቢያው ለሚገኙ ጤና ጣቢያዎች ማሳወቅ፡፡
5. በየእለቱ ቀጠሮ ካላቸዉ ተከራካሪ ወገኖች እና የፍ/ቤቱን ሌሎች አገልግሎት ፈልገው የሚመጡ ባለጉዳዮች ብቻ ወደ ፍ/ቤቱ ግቢ እንዲገቡ ማድረግ፡፡
6. በየደረጃው ባሉ ፍ/ቤቶች በሚወሰን ግዜ በመደበኛነት የኮቪድ 19 ተጋላጭነት ለመከላከል የፀረ-ተሀዋሲያን ርጭት ማከናወን፡፡
7. የፍ/ቤቱ አመራር የሚያወጣቸውን ተጨማሪ የጥንቃቄ እርምጃዎች በጥብቅ መተግበር ይሆናል፡፡
የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ለመከላከል በጤና ባለሙያዎች የሚሰጡ ምክሮችን በጥብቅ በመተግበር ከወረርሽኙ ራሳችንን፤ ቤተሰቦቻችንንና ሃገራችን ከችግር እንታደግ!!
----------------------- // ----------------------------
የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

ግልባጭ፡-
 ለክብርት ፕሬዝደንት ጽ/ቤት
ፌ/ጠ/ፍ/ቤት


ለሚዲያ ተቋማት በሙሉ
አዲስ አበባ

ዜና መግለጫ
በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከሀምሌ 13/2012 ዓ.ም ጀምሮ ስለሚሰጡ ተጨማሪ የዳኝነት አገልግሎቶች የተሰጠ መግለጫ
የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የኮሮና ቫይረስ (Covid-19) ወረርሽኝ በሀገራችን መኖሩ ከታወቀበት ጊዜ ጀምሮ የቫይረሱን ስርጭት ለመግታት የተለያዩ የጥንቃቄ እርምጃዎችን እየወሰዱ ይገኛሉ፡፡ ከመጋቢት 10 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ በከፊል ዝግ በመሆን እና የከፊል ዝግ ውሳኔውን በማራዘም እስከ ሐምሌ 10/2012 ዓ.ም ድረስ በፍ/ቤቱ አመራር በተለዩ ጉዳዮች ላይ ብቻ አገልግሎት እየሰጡ ቆይተዋል፡፡
ይሁን እንጂ ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ ባህሪና ወቅታዊ ሁኔታ አንጻር ወረርሽኙ በአጭር ጊዜ በቁጥጥር ውስጥ ልናስገባውና ስርጭቱን ሙሉ በሙሉ ልንገታው የማንችል መሆኑን እንዲሁም አብሮን በተግዳሮትነት የሚቀጥል እንደሆነ ማስረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ በመሆኑም ፍርድ ቤቶችን በከፊል በመዝጋት የዜጎች ፍትህ የማግኘት መብትን በውል ላልታወቀና ለተራዘመ ጊዜ ማቆየት የማይቻል መሆኑን ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ይረዳል፡፡ በተጨማሪም ከኮቪድ በኋላ ፍርድ ቤቶች መደበኛ ስራቸውን ይጀምሩ በሚባልበት ጊዜ ወደ ፍ/ቤት ሊመጣ የሚችለው ከፍተኛ የመዛግብት ፍሰት ፍርድ ቤቶች ስራቸውን መስራት የማይችሉበት ሁኔታ ውስጥ ሊያስገባቸው እንደሚችል በፍርድ ቤቱ የተከናወነው የመላምት ትንታኔ ያሳያል፡፡ ለእነዚህ ሁለት አበይት ችግሮች መፍትሄ መስጠት ያስችል ዘንድ ወረርሽኙን በከፍተኛ የመካላከልና የጥንቃቄ እርምጃዎችን በመውሰድ የተቋረጡትን አገልግሎቶች ደረጃ በደረጃ ማስጀመር አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡
ስለሆነም ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው እንዲቆዩ ከተደረጉበት ከሃምሌ 13 ቀን 2012 ዓ.ም በኋላ ደረጃ በደረጃ መደበኛ አገልግሎት መስጠት ስለሚጀምሩበት ሁኔታ ለፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት በአዋጅ ቁጥር 25/1988 አንቀፅ 16 (1) እና በዚሁ አዋጅ ማሻሻያ አዋጅ ቁጥር 454/97 አንቀፅ 4 በተሰጠው ስልጣን መሰረት ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ መመሪያ አውጥቷል፡፡
በመመሪያው መሰረት በየደረጃው ባሉ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከሃምሌ 13 2012 ዓ.ም ጀምሮ የሚሰጡ አገልግሎቶች እና የሚወሰዱ አስገዳጅ እርምጃዎች የሚከተሉት ይሆናሉ፡፡
1. ከሐምሌ 13 - 30 /2012 ዓ.ም የሚሰጡ አገልግሎቶች
 በሁሉም ደረጃ ባሉት ፍ/ቤቶች መልስ፣የመልስ መልስ፣ አስተያየቶች ፣የትዕዛዝ ውጤቶች ለመቀበል የተቀጠሩ፣ እልባት ለመስጠት ጥቂት ሂደት ብቻ የሚቀራቸው ጉዳዮች እንዲሁም እስረኛ ያላቸው መዛግብት በየቀጠሮ ቀናቸው የማስተናገድ፤
 ማስረጃ ለመስማት' ክስ ለመስማት የተቀጠሩ መዝገቦች በጣም አስቸኳይነታቸዉ በዳኛው፣ በየፍርድ ቤቱ በየደረጃው በሚገኝ አመራር እስካልታመነ ድረስ ለቀጣይ የ2013 በጀት ዓመት የሚቀጠር ይሆናል ሆኖም ግን ከዚህ በፊት በተሰጡት መመሪያዎች መሰረት ሲከናወኑ የነበሩ ተረኛ ችሎቶችን በማደራጀት በአመራሩ የተለዩ ወሳኝ እና አንገብጋቢ ጉዳዮች በተለይም ከዜጐች የሰብዓዊ መብት ጋር የተቆራኙ ጉዳዮችን፣ ከቤት ውስጥ ጥቃት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን፣ እግድ፣ በስምምነት ፍች፣ ጥፋት ውስጥ ገብተው የተገኙ ወጣቶች (ወጣት ጥፋተኞች)፣ የልጆች አስተዳደግ እና ቀለብን የመሠሉ የቤተሰብ ጉዳዮች፣ አፋጣኝ የወንጀል ጉዳዮች (RTD) ከአስቸኳይ ግዜ አዋጅ አፈፃፀም ጋር የተያያዘ የወንጀል ጉዳዮችን፣ በስምምነት ክስን ማቋረጥ፣ ከትላልቅ ሜጋ ኘሮጀክቶች ጋር የተያያዙ የንግድ ኢንቨስትመንት ጉዳዮች፣ ከሀገር ፀጥታ እና ሠላም ጋር የተያያዙ የወንጀል ጉዳዮች እንዲሁም ብዙ ተካራካሪ የሌላቸው መዛግብትን የሚስተናገዱ ሲሆን በመደበኛ ችሎት ሲስተናገዱ የነበሩ የስራ ክርክር፣ የሴቶች እና ህፃናት ችሎቶች፣ የሁከት እና ሌሎች የአስተዳደር ጉዳዮች በመደበኛ ችሎት ዳኞች በየቀጠሯቸው የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
 በየደረጃው ያሉ የፍርድ አፈጻጸም ችሎቶች በአጭርና በቀላሉ የሚፈፀሙ የአፈፃፀም ጉዳዮችን ማስተናገድ የሚጀምሩ ይሆናል፡፡ ከዚህ በተያያዘም በፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፍርድ አፈጻጸም ዳይሬክቶሬት ከሐምሌ 13/2012ዓ.ም ጀምሮ መደበኛ ስራውን የሚጀምር ሲሆን በፍርድ አፈፃፀም ምክንያት ከመኖሪያ ቤት ማስለቀቅ፣ የመኖሪያ ቤት ሽያጭ ማጫረት ማካሄድ ውስብስብነት ያላቸውና የሰዎች መሰባሰብ የሚጠይቁ የአፈፃፀም ጉዳዮች ተለዋጭ የስራ አቅጣጫ እስከሚሰጥ ድረስ ባሉበት ደረጃ እንዲቆዩ ይደረጋል፡፡
 የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በአዲስ አበባ ከሚገኙ ባለጉዳዮች የሚቀርቡ የሰበር አቤቱታዎችን የሚያሥተናግድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ከአዲስ አበባ ውጪ የሚገኙ ባለጉዳዮችን በዚህ ወቅት ማስተናገድ ለኮቪድ 19 ወረርሽኝ ያላቸውን ተጋላጭነት የሚጨምር መሆኑን ታሳቢ በማድረግ የወረርሽኙ ስርጭት አስጊነት በቀነሰና ፍርድ ቤቱ ተለዋጭ የስራ አቅጣጫ በሚሰጥበት ጊዜ የሚስተናገዱ ይሆናል፡፡
 በሁሉም ፍርድ ቤቶች የምርመራ መዛግብት የማጥራት ተግባር በተጨማሪነት የሚከናወን ይሆናል፡፡


የፌዴራልና የክልል ፍ/ቤቶች በመተባበር መንፈስ መስራታቸውን ይቀጥላሉ!

የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከክልል ፍርድ ቤቶች ጋር በጋራ ሊሰሩ የሚችሉበት ምህዳር እና የሚያገናኛቸው ሰንሰለት መነሻው ህግመንግስታዊ የዳኝነት ውክልና ስልጣናቸውና አስተዳደራዊ ግንኙነታቸውን ለመወሰን የወጡ ህጎች ናቸው፡፡

የኢፌዲሪ ህገመንግስት ስለፍርድ ቤቶች አወቃቀርና ስልጣን ግልጽ ድንጋጌዎችን ባስቀመጠበት ምዕራፍ ዘጠኝ የፌዴራል ከፍተኛና መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቶች ባልተደራጁባቸው ክልሎች የክልል ፍርድ ቤቶች የፌዴራል መጀመሪያና ከፍተኛ ፍርድ ቤቶች የዳኝነት ስልጣን በውክልና የተሰጣቸው መሆኑን ይደነግጋል፡፡ ከዚህ በመነሳት የክልል ፍርድ ቤቶች የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የሚመለከቷቸውን ጉዳዮች ከክልሉ የዳኝነት ጉዳዮች ጋር ደርበው ይሰራሉ፡፡ ለዚህም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለክልል ፍርድ ቤቶች የበጀት ማካካሻ እንደሚሰጥ ተጠቅሷል፡፡

ከዚህም በተጨማሪ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች የተሰጡ የመጨረሻ ውሳኔዎችን የማየት ስልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ይህም ፍርድ ቤቱ የፌዴራል ጉዳዮች ላይ በክልል ጠቅላይ ፍ/ቤቶች የተሰጡ ውሳኔዎችን በይግባኝ፤ የክልል ጉዳዮችን የተመለከቱ ውሳኔዎችን ደግሞ በሰበር ችሎት እንዲያይና ውሳኔውን እንዲያሻሽል ወይም እንዲያጸና ወይም እንዲሽር ያስችለዋል፡፡

በተመሳሳይ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የፌዴራል ፍርድ ቤቶችን አደረጃጀትና ዝርዝር የስልጣን ወሰን ለማስቀመጥ የወጣው የፌዴራል ፍርድ ቤቶች አዋጅ ቁ.25/1988 የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች ጋር በጋራ ስለሚያገናኟቸው ዳኝነታዊና አስተዳደራዊ ሁኔታዎች ያመላክታል፡፡ ከነዚህም መካከል የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የመዝገብ አያያዝና ጠቅላላ አሰራር ከክልል ፍርድ ቤቶች ጋር በመመካከር የሚሻሻልበትን ሁኔታ ያመቻቻል፡፡ የክልል ፍርድ ቤቶች የፌዴራል ጉዳዮችን አስመለክቶ ስላከናወኑት ተግባራት በስታትስቲክስ የተደገፈ ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያቀርባል፡፡

ከዚህም ባሻገር ዓዋጁ በሃገር አቀፍ ደረጃ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት፣ ምክትል ፕሬዝደንትና ዳኞች፤ የፌዴራል ከፍተኛና መጀመሪያ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝደንቶች፤ እና የክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንቶች አባል የሚሆኑበት እንዲሁም ሌሎች የፍትህ አካላት የሚሳተፉበት አንድ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ጉባዔ እንደሚኖር ይፈቅዳል፡፡ ይህ ጉባዔም በዳኝነት ስራ አስተዳደር ረገድ ባጋጠሙ ችግሮች ላይ ተወያይቶ መፍትሔ ይሰጣል፡፡ የፍርድ ቤቶችን አስራር ለማሻሻል የሚረዱ መመሪያዎችና ውሳኔዎችን ያሳልፋል፡፡ እንዲሁም አዳዲስ ህጎች እንዲወጡ ወይም ነባር ህጎች እንዲሻሻሉ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሃሳብ ያቀርባል፡፡

ሌላው የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በህገመንግስቱና ይህንኑ መሰረት በማድረግ በወጡ ዓዋጆች በተሰጣቸው የዳኝነት ስልጣን በማንኛውም ደረጃ የሚገኙ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የሚሰጧቸው ውሳኔዎችና ትዕዛዞች በክልል ፍርድ ቤቶች እንዲፈጸሙ የፌዴራሉ ፍርድ ቤቶች ማዘዝ እንደሚችሉም በግልጽ ተደንግጎ ይገኛል፡፡

ከላይ የተጠቀሱት መሰረታዊ የህግ ሃሳቦች የፌዴራልና የክልል ፍርድ ቤቶች የተሳሰሩ መሆናቸውንና የሚያገናኟቸው በርካታ ጉዳዮች እንዳሉ የሚያመላክቱ ናቸው፡፡ ህገመንግስቱ ስራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ የክልልና የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በህግ አግባብ የዳኝነት እየሰጡ ቆይተዋል፡፡ በሃገራችን የተዘረጋው ህገመንግስታዊና ፌደራላዊ ስርዓት ተጠናክሮ፤ የክልልና የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ዳኝነታዊ ነጻነታቸውን ጠብቀው ፍትህ የመስጠት ሃላፊነታቸውን እየተወጡም ናቸው፡፡ ነጻና ግልጽ፤ ህጋዊና ፍትሃዊ፣ ተደራሽና የህዝብ አመኔታ ያለው ዳኝነት ለመስጠት በየጊዜውና በየሁኔታው የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች ቢኖሩም ለጋራ ግብና ስኬታማነት የስልጣን ሚዛናቸውን ጠብቀው የየራሳቸውን ጥራት እያደረጉም ይገኛሉ፡፡

የፌዴራልና የክልል ፍርድ ቤቶች በውክልና እና በይግባኝ ስልጣናቸው የጋራ ባለጉዳዮች ሊኖሯቸው እንደሚችል የታመነ ነው፡፡ የዳኝነት ውክልና ስልጣን ባልተሰጣቸው ክልሎች እንኳን የፌደራል ፍርድ ቤቶች በተዘዋዋሪ ችሎቶች ዳኝነት ይሰጣሉ፡፡ በቪዲዮ ኮንፈረንስ እና በኢ ፋይሊንግ (የርቀት ችሎት ማእከሎች) በመታገዝም ባለጉዳዮች ባሉበት ከልል ሆነዉ አገልግሎት ማግኘት የሚያስችሉ አሰራሮችም ተዘርግተዋል፡፡ ይህም በክልል የሚገኙ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ባይ ባለጉዳዮችን ከአላስፈላጊ ወጪ እና እንግልት ለመታደግ ተችሏል፡፡

አስተዳደራዊ ጉዳዮችንም በተመለከተ በትብብር መንፈስ በጋራ ጉባዔ በመምከር፤ በመልካም ተሞክሮ እና በመረጃ ልውውጥ በመታገዝ በመካከላቸው መልካም የግንኙነት ባህል አዳብረዋል፡፡ በዳኝት አገልግሎት አሰጣጥና አስተዳደር ጉዳዮች ላይ በየጊዜው ምክክር ይደረጋል፡፡ የእርስ በእርስ የልምድ ልውውጥ ይካሄዳል፡፡ በሃገራችን ቀልጣፋ፤ ተደራሽ እና የሚሻሻል የዳኝነት አገልግሎት ለመስጠት የጋራ አቋም የተያዘባቸው የመረጃ ልውውጥ ስራዎችም ይከናወናሉ፡፡

በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ወደ ክልሎች እንዲሁም ከክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶች ወደ ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የሚላኩ ደብዳቤዎችና ማስታወሻዎች የመረጃ ልውውጥን ለማቀላጠፍ ጥቅም ላይ እንዲውሉ ከማድረግ በዘለለ የሚደረጉት የመረጃ ለውውጦች ተቋማዊና ክልላዊ አደረጃጀት ላይ ጣልቃ በመግባት አሉታዎ ተጽእኖ ለማሳረፍ ታስበው የሚደረጉ አይደሉም፡፡

በተለይም በሃገራችን የኮቪድ 19 ወረርሽኝን ስርጭት ለመግታትና ለመከላከል የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ባለበት ጊዜ ፍርድ ቤቶች የወረርሽኑ ማሰራጫ ማዕከል እንዳይሆኑ በመደበኛ አገልግሎት አሰጣጣቸው ላይ ለውጥ አድርገዋል፡፡ አስቸኳይነት ያላቸውን ጉዳዮች ብቻ እንዲያዩ በከፊል ዝግ ሆነው እንዲቆዩ በአመራሮቹ ውሳኔ ተላልፏል፡፡ በዚህ ውሳኔ ለፌዴራል ፍርድ ቤቶች የወረዱ የስራ አቅጣጫዎችን በደብዳቤ /በማስታወሻ / የክልል ፍርድ ቤቶችና ባለጉዳዮች እንዲያውቋቸው ማድረግ አስፈላጊነቱ አጠያያቂ አይሆንም፡፡ የክልል ባለጉዳዮች ወደ አዲስ አበባ በመምጣት እንግልት እንዳይደርስባቸውና ለወረርሽኙ ተጋላጭ እንዳይሆኑ ያግዛል፡፡ የክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤቶችም በፌዴራል ፍርድ ቤቶች ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ተረድተውና ተገንዘብው በፍርድ ቤቶቻቸው የአሰራር ለውጥና ማሻሻያ እንዲሁም አስተዳደራዊ አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ ይረዳቸዋል፡፡ ይህም የመረጃ ልውውጥ የክልልም ሆነ የፌዴራል ፍርድ ቤቶቹ የጋራ የዳኝነት ተልዕኳቸውን በተጣጣመና በተናበበ መልኩ እንዲወጡ መልካም እድል ይፈጥርላቸዋል፡፡

በአጠቃላይ በፌደራልና በክልል መንግስታት ህግ የመተርጎምና ዳኝነት የመስጠት ተልዕኮ የተሰጣቸው ፍርድ ቤቶች በህገመንግስቱ እና ህገመንግስቱን መሰረት አድርገው በወጡ አዋጆች ዜጎች ህጋዊና ፍትሃዊ ዳኝነት የማግኘት መብቶቻቸው እንዲከበሩባቸው በመተባበር መንፈስ መስራታቸውን ይቀጥላሉ፡፡

አካላዊ ርቀታችንን በመጠበቅ፤ አፍና አፍንጫችንን በጭምብል በመሸፈን፤ እጃችንን በሳሙናና በውሃ በተደጋጋሚ በመታጠብ፤ (በተቻለ መጠን) በቤት በመቀመጥ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን በጋራ እንከላከል!

ፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት


የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው የሚቆዩበትን ጊዜ

ለተጨማሪ 30 የስራ ቀናት አራዘሙ፡፡

የኮሮና ቫይረስ (ኮቪድ-19) ወረርሽኝን ስርጭት ለመግታት የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከመጋቢት 10 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ግንቦት 30 ቀን 2012 ዓ.ም በከፊል ዝግ ሆነው እንዲቆዩና አስቸኳይነት ያላቸውን ጉዳዮች ብቻ በተረኛ ችሎት እንዲመለከቱ መደረጉ ይታወቃል፡፡

የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ፕሬዝደንቶችና ም/ፕሬዝደንቶች በፍርድ ቤቶች እየተሰጠ ያለውን አገልግሎት እና የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ስርጭትን ወቅታዊ ሁኔታ ባካሄዱት ስብሰባ ገምግመዋል፡፡

የወረርሽኙ ስርጭት እየተስፋፋ በመምጣቱ ምክንያት ቫይረሱ የተገኘባቸው ሰዎች ቁጥር በየጊዜው እየጨመረና የስርጭት አድማስም እየሰፋ መምጣቱን የጤና ጥብቃ ሚኒስቴር በየጊዜው ከሚያስራጫቸው መረጃዎች የፍርድ ቤቱ አመራር መገንዘብ ችሏል፡፡

አመራሩ ባካሄደው ስብሰባ የዳኝነት አገልግሎት ለማግኘት ከክልሎች፣ ከአዲስ አበባና ከድሬዳዋ ከተሞች ወደ ፍርድ ቤቶች የሚመጡ ባለጉዳዮች ቁጥራቸው በርካታ በመሆኑና የእነዚህ ባለጉዳዮች ለቫይረሱ ስርጭት ያላቸወን ተጋላጭነት ለመቀነስ እንዲሁም ዳኞችና ድጋፍ ሰጭ ሰራተኞች ደህንነታቸው በተጠበቀ ሁኔታ ስራቸውን እንዲያከናውኑ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን በማመን የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከሰኔ 1 ቀን 2012 ጀምሮ እስከ ሀምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም ለተጨማሪ 30 የስራ ቀናት በከፊል ዝግ ሆነው አንዲቆዩ ወስኗል፡፡

ፍ/ቤቶች ዝግ ሆነው በሚቆዩበት ጊዜ በተረኛ ችሎት እንዲታዩ ከተለዩት ጉዳዮች በተጨማሪ አነስተኛ የተገልጋይ ቁጥር ያላቸው ሌሎች የዳኝነት አገልግሎት ሊሰጥባቸው የሚችሉ የጉዳዮችን በመለየት አገልግሎቱን በየጊዜው ቀስ በቀስ ለባለጉዳዮች ክፍት እየተደረገ እንዲሄድ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑንም በአመራሩ ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ ይህን መሰረት በማድረግም ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው በሚቆዩባቸው ጊዜ፡-

1. ከሰኔ 30/2011 ዓ/ም በፊት የተከፈቱ ዉዝፍ ይግባኝ መዝገቦችን ለመወሰን በችሎት ባለጉዳዮችን የመስማት አስፈላጊነት የታመኑባቸው ጉዳዮች ተለይተው ውሳኔ እንዲሰጣቸው ይደረጋል፡፡

2. የወንጀል ይግባኝ ጉዳዮችን በተመለከተ ከማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ጋር የቪዲዮ ኮንፈረንስ መርሃ ግብር በማዘጋጀት ተከራካሪ ወገኖች ይሰማሉ፤ እንደየሁኔታው ከባለጉዳዮች ጋር በመነጋገር የቃል ክርክራቸውን በጽሁፍ የሚያቀርቡ ሲሆን ወሳኔ እንዲያገኙም ይደረጋል፡፡

3. የፍታብሔር ይግባኝ ጉዳዮችን በተመለከተ ባለጉዳዮችን መስማት አስፈላጊነቱ በዳኞች ከታመነባቸው ጉዳዮች ውጭ የሆኑ መዛግብት እልባት እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡

4. አስቸኳይ በሆኑ ጉዳችዮች በተረኛ ችሎት የተሰጠውን ትዕዛዝ፣ ብይን እና ውሳኔ መሰረት በማድረግ የሚቀርቡ የይግባኝ ጉዳዮች በአፋጣኝ እልባት የሚሰጣቸው ይሆናል፣

5. አስቸኳነት ያላቸው ጉዳዮች ማለትም ከህጻናት ቀለብና አስተዳደግ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች፣ የዋስትና ጉዳይ፣ የአሰሪና ሰራተኞች ጉዳይ፣ በሴቶችና ህፃናት ላይ የሚፈጸሙ የቤት ውስጥ ጥቃቶች እና ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈጸሚያ መመሪያ ወይም ደንብ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን የሚመለከቱ ይሆናሉ፡፡

6. የፌዴራልና የክልል ጉዳዮች ውሳኔን መሰረት በማድረግ ተከፍተው በሂደት ላይ የነበሩ የአፈጻጸም ጉዳዮች የስራና አፈጻጸም አቅጣጫ እስከሚሰጥባቸው ጊዜ ድረስ በደረሱበት ደረጃ ቆመው የሚቆዩ ይሆናል፡፡

7. በየደረጃው ባሉ ፍርድ ቤቶች ተዘጋጅቶ በሚገለጸው መርሃ-ግብር መሰረት የውሳኔ፣ የትዕዛዝ፣ የብይንና የመዝገብ ግልባጭ የመስጠት ተግባር የሚከናወን ይሆናል፡፡

የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ስርጭት ለመከላከል ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ በሆኑባቸው ጊዜያት ወደ ፍርድ ቤቶቹ ቅጥር ጊቢ የሚገቡና የሚስተናገዱት ባለጉዳዮቹ ብቻ ይሆናሉ፡፡ ባለጉዳዮች ለአገልግሎት ወደ ፍርድ ቤት ሲመጡም የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል መልበስ እንዲሁም በመግቢያ በር ላይ በተዘጋጀ እጅ መታጠቢያ እጃቸውን መታጠብ ይጠበቅባቸዋል፡፡ የእርስ በእርስ ርቀታቸውንም ጠብቀው እንዲስተናገዱ የፍርድ ቤቱ አመራር አሳስቧል፡፡

የመከላከያ ጥንቃቄዎችን በአግባቡ በመተግበር ወረርሽኙ ከሚያደርሰው አስከፊ ጥቃት ህብረተሰቡ አራሱን እንዲከላከል የፌዴራል ፍርድ ቤቶች መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት


በአሰራር ሂደት የሚከሰቱ ስህተቶች ለዳኝነት ነጻነት አለመኖር ማሳያ ተደርገው ሊወሰዱ እንደማይገባ የፍርድ ስራ ምርመራና ኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት ገለጸ፡፡
ሰሞኑን በማህበራዊ ትስስር ገጾች ለጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ሰበር አጣሪ ችሎት በቀረበ አንድ የፍትሐ-ብሔር ጉዳይ ላይ በአመራሩ ጣልቃ ገብነት ሁለት ጊዜ የተለያየ ውሳኔ እንደተሰጠ ተደርጎ እየተሰራጨ ያለው መረጃ በፍርድ ቤቱ ዳታ ቤዝ ባለሙያዎች በተፈጠረ የአሰራር ስህተት ምክንያት መሆኑን ጉዳዩን ያጣራው የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት የፍርድ ስራ ምርመራና ኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት ገልጿል፡፡
በፍርድ ቤቱ አመራር ጣልቃ ገብነት የዳኝነት ነጻነት አደጋ ላይ ወድቋል እየተባለ በማህበራዊ ትስስር ገጽ ላይ መረጃ እየተሰራጨ መሆኑን ጥቆማ የደረሰው የጠቅላይ ፍ/ቤቱ የፍርድ ስራ ምርመራና ኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት ጉዳዩን ለማጣራት ባካሄደው ምርመራ የዳታ ቤዝ ባለሙያዎች የሰበር አጣሪው ችሎት በአምስት ዳኞች ውሳኔ የሰጠበትን ጉዳይ ቀደም ሲል “አያስቀርብም” ለማለት በመዝገቡ ውስጥ ተያይዞ የቀረበን ቅጽ በመመልከት ውሳኔ እንደሰጠ የሚገልጽ የተሳሳተ መረጃ በመረጃ ቋት (Database) ውስጥ በማስገባታቸው ምክንያት የተፈጠረ ችግርን መነሻ በማድረግ መሆኑን አረጋግጧል፡፡
የፍርድ ቤቱ የፍርድ ስራ ምርመራና የኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት ችግሩን የፈጠሩት ባለሙያዎችንና የችግሩን ስረ ነገር ለመለየት የማጣራት ስራውን የቀጠለ ሲሆን በዚህ ያልተገባና ሃላፊነት በጎደለው ተግባር ላይ ድርሻ ያላቸው ባለሙያዎች ለተፈጠረው ስህተት በዲሲፕሊን እንዲጠየቁና በፍርድ ቤቱ በተዘረጋው የተጠያቂነት ስርዓት ተገቢው አስተዳደራዊ እርምጃ እንዲወሰድባቸው የሚያደርግ መሆኑን ገልጿል፡፡
ህብረተሰቡም የዳኝነት ነጻነት የለም፤ የዳኝነት አካሉ አሁንም ከጣልቃ ገብነት ነጻ አልወጣም እየተባለ በማህበራዊ ትስስር ገጾች የሚተላለፈው መረጃ ከእውነት የራቀና መሰረት የሌለው መሆኑን ተረድቶ በዳኝነት አካሉ ላይ የሚሰነዘሩ ማናቸውም አስተያየቶችና የሚቀርቡ ትችቶችን በጥንቃቄ እንዲመዝናቸው ጠይቋል፡፡ ፍርድ ቤቶች ዜጎች ፍትህ ለማግኘት ጠንካራ ተስፋ የሚጥሉባቸው ተቋማት ናቸው ያለው ዳይሬክቶሬቱ የፍ/ቤቶች መልካም ገጽታን የማጠልሸትና የህዝቡን አመኔታ በመሸርሸር አሉታዊ ውጤት ያላቸው መረጃዎችን በማንጨት የሚያሰራጩ አካላት ከድርጊታቸው ቆም ብለው ጥቅምና ጉዳቱን እንዲያመዛዝኑም መክሯል፡፡ የምርመራና ኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት የደረሰበትን የምርመራ ውጤትም እንዲህ አብራርቷል፡፡
ጉዳዩ በጀ ፎር ኮንስትራክሽን እና አስማማው ኃ/የተ/የግ/ማህበር መካከል ከስር ፍርድ ቤት ጀምሮ የውል ክርክር ሲደረግበት የቆየ ነው፡፡ አመልካች ለጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ህዳር 10 ቀን 2012 ዓ.ም ባቀረበው አቤቱታ የፍርድ ቤቱ ይግባኝ ችሎት ዳኝነት በጠየቁበት ጉዳያቸው ላይ የሰጠው ውሳኔ የህግ ትርጉም ስህተት ያለው መሆኑን ጠቅሰው የሰበር ችሎቱ ጉዳዩን አይቶ እንዲያርምላቸው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ የአቤቱታውን ተገቢነት እንዲያጣራ በመዝገብ ቁጥር 185837 ጉዳዩ የቀረበለት 1ኛ ሰበር አጣሪ ችሎት ጥር 8 ቀን 2012 ዓ.ም በዋለው ችሎት ጉዳዩን ሰምቷል፡፡ ይህንንም ተከትሎ በጉዳዩ ላይ የችሎቱ ሁለቱ ደኞች የውሳኔ ሃሳብ ያቀረቡበት እና አንድ ዳኛ ግን በጉዳዩ ላይ እንነጋገርበት ማለታቸውን የሚያሳይ የካቲት 30 ቀን 2012 ዓ.ም የተሞላ የውሳኔ ቅጽ ተያይዟል፡፡ በዚህም ምክንያት ችሎቱ ውሳኔ ያልሰጠ መሆኑን መዝገቡ ያስረዳል፡፡
አቤቱታ አቅራቢው ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝደንት ጉዳያቸው ውሳኔ ሳይሰጠው ረጅም ጊዜ መውሰዱን፤ መዝገባቸውም ቀጠሮ ሳያገኝ መቆየቱንና በዚሀም ምክንያት ጉዳያቸው በምን ደረጃ ላይ እንደለ መረጃ ማግኘት ያልቻሉ መሆኑን ጠቅሰው መጋቢት 14 ቀን 2012 ዓ.ም በጽሁፍ አቤቱታ ያቀርባሉ፡፡ የፍርድ ቤቱ ፕሬዝደንትም ችሎቱ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ያደርጋሉ፡፡ ከችሎቱ ዳኞች ጋርም ባካሄዱት ውይይት ክብርት ፕሬዝደንቷ በአዋጅ ቁጥር 25/88 አንቀጽ 21 (1) በተሰጣቸው ስልጣንና በችሎቱ ዳኞች ስምምነት ጉዳዩ በሶስት ዳኞች ከሚታይ ይልቅ በአምስት ዳኞች እንዲታይ የስራ መመሪያ ይሰጣሉ፡፡
አምስቱ ዳኞችም መዝገቡን መጋቢት 29 ቀን 2012 ዓ.ም አስቀርበው ጉዳዩን መርምረዋል፡፡ በመጨረሻም ሰበር ችሎቱ ይግባኝ ሰሚው ችሎት በሰጠው ውሳኔ ላይ ሊያያቸው የሚገቡ ዝርዝር ጉዳዮች ያሉበት ነው በማለት “ያስቀርባል” የሚል ውሳኔ በአብላጫ ድምጽ ያሳልፋል፡፡
በዚህ ሂደት መዝገቡ ሚያዚያ 2 ቀን 2012 ዓ.ም ወደ ዳታ ቤት በመሄዱ የዳታ ቤዝ ባለሙያዎች መጀመሪያ የውሳኔ ሃሳብ የቀረበበትን ነገር ግን ውሳኔ ያላረፈበትን ቅጽ በመመልከት ጉዳዩ “አያስቀርብም” ተብሎ መወሰኑን የሚገልጽ መረጃ መረጃ ቋት (Database) ውስጥ በስህተት ያስገባሉ፡፡ ይህም መረጃ ለባለጉዳዮች በ992 አጭር የጽሑፍ መልዕክት ይደርሳቸዋል፡፡ ባለጉዳዮቹም ውሳኔውን ተቀብለው በዝምታ ያልፋሉ፡፡ በሌላ በኩል በበችሎቱ ውሳኔ መሰረት በሪጂስትራር በኩል የአመልካች የሰበር አቤቱታ ከፍርድ ቤቱ መጥሪያ ጋር ለተጠሪ እንዲደርስ በታዘዘው መሰረት መጥሪያው እንዲደርስ ተደርጓል፡፡
የተፈጠረውን ስህተት ለማረም በመረጃ ቋት (Database) በገባው ትክክለኛ መረጃ መሰረት ለባለጉዳዮቹ መዝገቡ ያስቀርባል ተብሎ መወሰኑን እንዲሁም ለምርመራ እና የመልስ መቀባበያ ቀጠሮ መሰጡተን የሚገልጽ መረጃ በ992 አጭር የጽሁፍ መልእክት በድጋሚ ይደርሳቸዋል፡፡
በአንድ ጉዳይ ላይ አንድ ችሎት በተለያየ ጊዜ የተለያየ ውሳኔ እንዴት ሊሰጥ ይችላል የሚል ተገቢነት ያለው ጥያቄ ምናልባትም ከግራና ቀኝ ተከራካሪ ባለጉዳዮች መካከል አንዱ ያነሳሉ፡፡ ለዚህም ጥያቄ አሁን ላይ ማንነታቸው ተለይቶ ያልታወቁ አካላት ያልተገባና እውነታነት የሌለው ምክንያት በመስጠት የዳኝነት ነጻነት በአመራሩ ጣልቃ ገብነት መጣሱንና የውሳኔ ለውጥ መደረጉን የሚገልጽ መረጃ መሰራጨት መጀመሩን የምርመራ ክፍሉ አመልክቷል፡፡ ነገር ግን አቤቱታ አቅራቢው ባለጉዳይ ከላይ እንደተገለጸው ለፍርድ ቤቱ ፕሬዝደንት ጽ/ቤት ያቀረቡት አቤቱታ ውሳኔ ዘገየብኝ፤ መዝገቡም ቀጠሮ ባለመያዙ ጉዳያቸው ያለበትን ደረጃ ማወቅ አለመቻላቸውን የሚገልጽ መሆኑን ከመዝገቡ ጋር የተያያዘው ማስረጃ ያሳያል፡፡
ይህን አይነት የተለመደ አቤቱታ የመቀበልና አስተዳደራዊ መፍትሄ የመስጠት አሰራር በተሳሳተ ግንዛቤ ዓላማውን እንዲስት በማድረግ አቤቱታው ውሳኔ እንዲሻሻል የቀረበ በማስመሰልና ከእውነት የራቀ መረጃ በማሰራጨት ላይ መሆናቸውን የምርመራ ክፍሉ ጠቁሟል፡፡
ዳይሬክቶሬቱ በዲሲፕሊን የሚጠየቁ አካላትን ለይቶ ተገቢው አስተዳደራዊ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ የሚያደርግ መሆኑን በማረጋገጥ ጉዳዩን ለማጣራት የሚፈልግ ማንኛውም ግለሰብም ሆነ ተቋም የመዝገቡን ሙሉ ግልባጭ በማግኘት ማጣራት እንደሚችል ጨምሮ ገልጿል፡፡
የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት


የፌዴራል ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው የሚቆይቡት ጊዜ ተራዘመ
የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የኮሮና ቫይረስ (COVID 19) ስርጭትን ለመከላከል ቀጣይ የጥንቃቄ እርምጃዎችን መውሰድ በማስፈለጉ ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው የቆዩበትን ጊዜ ለተጨማሪ 22 የስራ ቀናት አራዘመ፡፡
የፌዴራል ፍርድ ቤቶች ከመጋቢት 10 /2012 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሚያዚያ 30 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ በከፊል ዝግ ሆነው አፋጣኝ የፍርድ ቤት ውሳኔና ትእዛዝ የሚፈልጉ ገዳዮችን በተረኛ ችሎቶች በማስተናገድ አገልግሎት እንዲሰጡ መወሰኑ ይታወቃል፡፡
በዚህ ጊዜ የፌዴራል ዳኞች በየምድብ ችሎቱ በተደራጁ ተረኛ ችሎቶች እየሰሩ ቆይተዋል፡፡ በቤትና በቢሮ ለውሳኔ፤ ለብይንና ለትዕዛዝ የተቀጠሩ መዛግብትን በማቃለል ከፍተኛ ውጤት በማስገኘት ላይም ናቸው፡፡ በተጨማሪም የተረኛ ዳኞችን ቁጥር በመጨመር ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ጋር ተያይዞ የሚቀርቡላቸውን ጉዳዮች በመስራት ላይ ሲሆኑ በተሰጡ ውሳኔዎች ላይ የሚቀርቡ የይግባኝ አቤቱታዎችም በየደረጃው ባሉ ፍርድ ቤቶች በመታየት ላይ ናቸው፡፡
ዓለምን እያስጨነቀ ያለው የኮሮና ቫይረስ (COVID 19) ወረርሽኝ በሃገራችን ስርጭቱ እንዳይስፋፋ ለመገደብ እየተወሰደ ያለው የጥንቃቄና የመከላከል ስራ አሁንም ትኩረት የሚፈልግና ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት በመንግስት እየተገለጸ ይገኛል፡፡ ይህንንም ጥረት ለማገዝና በየዕለቱ በትንሹ 18 ሺህ ያህል ባለጉዳዮች የሚስተናገዱባቸውን ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ማድረግ ባለጉዳዮች በቤት እንዲቆዩና አካላዊ ርቀትን እንዲጠብቁ ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ከግንቦት 3/2012 ዓ.ም ጀምሮ ለ22 የስራ ቀናት ማለትም እስከ ግንቦት 30/2012 ዓ.ም ድረስ አሁንም ለሶስተኛ ዙር በከፊል ዝግ ሆነው እንዲቆዩ ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ወስኗል፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ፡-
• በየፍርድ ቤቱ ለምርመራ እና ለውሳኔ የተቀጠሩ ውዝፍ መዛግብት ተለይተውና እንደየሁኔታው ታይተው እልባት የሚሰጣቸው ይሆናል፡፡ ውዝፍ መዛግብት የሌለባቸው ችሎቶች ውዝፍ መዛግብት ያለባቸውን ችሎቶች እንዲያግዙ ይደረጋል፡፡
• በማረሚያ ቤት ያሉ ባለጉዳዮችን በተመለከተም ከማረሚያ ቤት አስተዳዳሪዎች ጋር በመወያየትና መርሃ ግብር በማዘጋጀት በቪዲዮ ኮንፈረንስ አገልግሎት ለመስጠት ጥረት ይደረጋል፡፡
• ፍርድ ለተሰጠባቸው ጉዳዮች በቂ የውሳኔ ግልባጮች ከወዲሁ ተዘጋጅተው ባለጉዳዮችን እንዲጠብቁ ይደረጋል፡፡
• ባለጉዳዮች በአካል ፍ/ቤት ቀርበው በመደበኛው አካሄድ የመሰማት እድል ሊሰጣቸው ይገባል የሚያስብሉ ጉዳዮች ሲያጋጥሙ በሪጅስትራር ተለይተውና የሚመለከተውን አካል በማስፈቀድ ተግባራዊ የሚደረግ ይሆናል፡፡
• አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ለማስፈጸም ተግባራዊ እየተደረጉ ካሉ መመሪያዎች ጋር በተያያዘ የሚቀርቡ ጉዳዮች በአፋጣኝ እልባት ማግኘት የሚገባቸው በመሆኑ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በተረኛ ችሎቶች የዳኞች ቁጥር እንዲጨምር ይደረጋል፡፡ ከእነዚህ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ የሚቀርቡ የይግባኝ አቤቱታዎችም በአፋጣኝ ታይተው እልባት የሚሰጣቸው ይሆናል፡፡
ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ በሰጠው የስራ አቅጣጫ እጅግ አስገዳጅ አገራዊና ኢኮኖሚያዊ እንድምታ ያላቸው አስቸኳይ መፍትሄ ለሚፈልጉ ብርቱ ጉዳዮች እንደ ሁኔታው በየደረጃው የሚገኙ የፍ/ቤት አመራሮች እና የጉዳዮች ፍሰት አስተዳደር ኃላፊዎች ፈጣን ምላሽ እንዲሰጡ አሳስቧል፡፡ እንዲህ ያሉ ጉዳዮች መታየት ሲኖርባቸውም ከሚኒስትሮች P COVID Task Force አስፈላጊው ፈቃድ እንደሚጠየቅም ገልጿል፡፡
በተመሳሳይ ወደ ፍርድ ቤት በአካል የሚመጣ ማንኛውም ሰው የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ጭንብል (Mask) ማድረግ ግዴታ መሆኑን፤ እጅን በተዘጋጀ ንጽህና መጠበቂያ ውሃና ሳሙና መታጠብ እንዳለበት እንዲሁም በባለሙያዎች እና በተገልጋዮች መካከል፤ በአገልግሎት ሰጪ እና አገልግሎት ተቀባይ መካከል ያለውን አካላዊ ርቀት መጠበቅ እንደሚገባም ፍርድ ቤቱ ባሳለፈው ውሳኔ ጨምሮ አሳስቧል፡፡
============= // ============
https://www.facebook.com/The-Federal-Supreme-Court-of-Ethiopia-265784033571676/?__tn__=kC-R&eid=ARCO5D2C29ldENOA65_tSWVap4TZFnMPrZtHeNbTJaTU0948NPkb9CuK72CjP8VKq7vB4eXdMsaae605&hc_ref=ARTfTfNijGxLWI7qB6KR797Dy3qG5HGQ2Tvo8s1tfaTDp8zqK_LC5vbMx_9Z7t52hXA&fref=nf&__xts__%5B0%5D=68.ARAwJ82Sla185RZLoWueyWnYSKpFnCSbs8c30sFADTDpAEWCbAzXREXh88nz3vyPkXX9hAylPTHOI4Hzi5bulZ_NHhHXpowZh0QmntGX8vaerlxO0pPRcFNqqRBmPa_uZ7HajcnzUoRrjSdHABcdb8Lze5_tCN3kTbHihx3iK8omlH-v7HkNOyC4-Z91Q2-AigchwdEBVHHqBZuH96C__WpiXXydr5fkqmYEverbtjaUxk7T_ohNFnvMghKsdmUfmlqftvgsH-n7y9_gB88ZNcUmZwukDWfEvuI3jBDPoYIVHQD4rMKbxERWLYopi2DncqrnxWcsQ9SQk88PFGp9xwbfQg
የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት






የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የኮሮና ሻይረስ ስርጭትን ለመግታት መንግስት ያወጣውን የአስቸኴይ ጊዜ አዋጅ ትከትሎ ይፋ የተደረገውን ማስፈጸሚያ ድንብ ተላልፈዋል በሚል በዐቃቤ ህግም ሆነ በሌላ የሚቀርቡ ጉዳዮችን በየምድብ ችሎቶቹ በተደራጁ ተረኛ ችሎቶች የሚያስተናግዱ ይሆናል፡፡


FSC decided files.pdf
5.0Mb
የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል በከፊል ዝግ ሆነው በቆዩባቸው ጊዜያት የፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ከመጋቢት 11- 30 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ በተለያዩ ችሎቶች በቀረቡ መዝገቦች ላይ የተሰጡ ውሳኔዎች የሚገልጽ መረጃ እንዲህ ቀርቧል፡፡
የፌ/ጠ/ፍ/ቤት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

20 last posts shown.

2 685

subscribers
Channel statistics