ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ አትበሉኝ ሲል ተናግሯልን ?
በክርስቶስ ስም እጅግ በጣም ሩኅሩህ በጣም አዛኝ በኾነው።
ለስም አጠራሩ ክብር ምሥጋና ይግባውና የጌታችን ክርስቶስን አምላክነት መቃወም የዕለት ግብራቸው ያደረጉት ተንባላት መጽሐፍ ቀመስ ያልሆነውን ምዕመን ግራ ለማጋባት ከመጽሐፍ ቅዱስ በመጥቀስ መቅጠፍ ልምዳቸው ነው ፤ ታዲያ በዚህ ጥርሳቸውን በነቀሉበት የማሳሳት ተግባር ከከንፈራቸው የማይለዩት አንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል አለ። ጥቅሱም እንዲህ ይነባል፦
“በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም።” (ማቴ 7:21)
ታዲያ ሙስሊሞች ይህን የጌታ ንግግር ይጠቅሱና “
ኢየሱስን ይሉታልን? ይህ ከሆነ መንግስተ ሰማያት መግባት አይፈልገጉም ማለት ነው። ... ኢየሱስን የሚለው ማን ነው? ሙስሊሞች ወይስ ክርስቲያኖች? 'አላውቃችሁም ፣ እመሰክርባቸዋለሁ' ያለውስ ማንን ነው? ክርስቲያኖችን! ... እና መንግስተ ሰማያት መግባት አይፈልጉም? ለምን ሌላ ትርጉም በመስጠት ራስዎን ያታልላሉ?... ታዲያ እንዴት ተታለሉ?” [1] ይሉናል ለመሞገት እየቃጣቸው።
በእውነቱ ሌላ ትርጉም የሰጠው ፣ ራሱንስ ያታለለው ማን ነው ? የሚለውን በዚህች መጣጥፍ አመልክተን ፣ ከዚያም ሻገር በማለት በጠቀሱት ጥቅስ የጌታችን እና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት አሳይተን እንቋጫለን - መልካም ንባብ !
ጅማሯችንን ክፍሉ የሚገኝበትን ዓውድ ከመገምገም እናድርግ ፤ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 7:21 የተራራው ስብከት ተብሎ በሚጠራው የወንጌል ክፍል ውስጥ የሚገኝ ሲሆን በማቴዎስ ወንጌል ከምዕራፍ 5 እስከ 7 ያለውን የሚሸፍን ፣ ጌታችን ለሐዋርያት ክርስቲያናዊ ምግባርን ያስተማረበት ክፍል ነው።
ይህን በአዕምሯችን ይዘን ሙስሊሞቹ ከሚጠቅሱት ክፍል ቀደሞ የተቀመጡትን የጌታ ቃሎች ስንመለከት በቁጥር 15 ላይ እንዲህ ይላል፦
“የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡባችሁ በውሥጣቸው ግን ነጣቂዎች ተኵላዎች ከሆኑ ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ።” ፤ እነዚህ ተኩላዎች ብሎ የጠራቸው ሐሰተኛ ነቢያቶችን ከእውነተኛዎቹ እንዴት እንደምንለያቸው ሲናገር ደግሞ ቁጥር 20 ላይ "
ስለዚህም ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ" ብሏል።
ቀጥሎም ቀደም ብሎ ከሐሰተኞች ነብያት እንድንጠነቀቅ የነገረን በማጽናት ጌታችን
“በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ የሚለኝ ሁሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም” ሲል አክሏል ፤ በዚህም ከዚህ በመነሳት ጌታችን ፍሬ ስለሌላቸው (እምነቱን ይዘውት ነገር ግን ምግባራቸው እሾህ ስለሆነ ሰዎች) እየተናገረ እንጂ በጠቅላላው ስለ ሁሉም ህዝበ ክርስቲያኑ እያወሳ አለመሆኑን መገንዘብ እንችላለን።
እንዲሁም ይህንኑ ጥቅስ በተቃራኒ ንባብ (
contrario reading) ስናነብ
"... ጌታ ሆይ ፣ ጌታ ሆይ ..." የሚለው የጌታ ቃል ምግባረ ብልሹ በከንፈራቸው ብቻ አማኞች የሆኑት የሚመለከት ሲሆን ይሄ አስተብቅዖታቸው የማይሰማው ስለ ምግባራቸው ብልሹነት ነው ፤ ማለትም ጥቅሱ በተቃራኒ ንባብ ሲነበብ የቀና ፣ በጎ እና ፍሬያማ ምግባር ያላቸው ክርስቲያኖች
"... ጌታ ሆይ ፣ ጌታ ሆይ ..." ቢሉ መንግስተ ሰማያት መግባት ይችላሉ ፣ ስህተት ውስጥም አልወደቁም እንዲሁም ክርስቶስ በሚገባ
«ጌታ» ተብሎ ይጠራል የሚል ነጥብ ያስይዛል።
እጅን በአፍ የሚያስጭነው ደግሞ የክርስቶስን አምላክነት ለመቃወም በጠቀሱት ማቴ 7:21 ላይ
"... ጌታ ሆይ ፣ ጌታ ሆይ ..." የሚለው ቃል ባስተውሎ ከተመለከትነው የክርስቶስን አምላክነት ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ መሆኑ ነው ፤ እንዴት ? በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር አምላክ በዕብራይስጥ ቋንቋ
"አዶናይ ያሕዌ/ጌታ እግዚአብሔር" እየተባለ ይጠራ የነበረ ሲሆን [2] ሰብአ ሊቃናት
"አዶናይ ያሕዌ(אֲדֹנָי יַהְוֶה)" የሚለውን ቃል ወደ ግሪክ
"κύριε κύριε/ጌታ ጌታ" ብለው ተርጉመውታል - ይህም አምላክነትን የሚያሳይ ሲሆን ለአምላክ ብቻ የሚውል መጠሪያ ነው።
በዚህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴ 7:21 እና 25:11 ላይ ይሄንኑ አገላለጽ መጠቀሙ አምላክነቱን ይገልጣል ፤ ይህን በተመለከተ በዘመናዊ የሐድስ ኪዳን ጥናት ፕሮፌሰር የሆነው Charles L.Quarles በማቴዎስ ወንጌል ማብራሪያው ላይ እንዲህ ይላል፦
"ድርብ ጥሪ የሆነው ‘κύριε κύριε’ የኢየሱስን አምላክነት እውቅና የሚሰጥ ሆኖ ተቀምጧል። ይህ ድርብ ጥሪ በሰባ ሊቃናት ትርጉም (LXX) ውስጥ አሥራ ስምንት ጊዜ ተጠቅሷል ፤ ሁልጊዜም ያህዌን ለመጥቀስ እና በተለምዶም የመለኮታዊው ስምና ማዕረግ የሆነውን ‘አዶናይ ያህዌ’ን ለመተርጎም ያገለግል ነበር።” [3]
ነገር ግን አንዳንዶች ይህን አረዳድ በመቃረን
"...ጌታ ሆይ ፣ ጌታ ሆይ ..." የሚለው በብሉይ ኪዳን
"አዶናይ ያሕዌ" የሚለው በግሪክ ሲገለጽ ሳይሆን በቀላሉ ልመናን ፣ የስሜት መሰበርን የሚያመለከት ነው በማለት ይሞግታሉ ፤ Jason A. Staples የተባለው ሊቅ
"...ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ ..." የሚለውን ሀረግ በተመለከተ የሚቀርቡ ከላይ ያነሳነውንና ሌሎች አረዳዶችን ከመዘነ በኋላ ሀረጉን እንዴት መረዳት እንደሚገባን እንዲህ በማለት ይደመድማል፦
"
የ ‘κύριος’ ድርብነት እና እነዚህ አባባሎች በማቴዎስና በሉቃስ ውስጥ ጥቅም ላይ የዋሉበትን መንገድ ስንመለከት፣ እነዚህ ጥቅሶች ኢየሱስ ራሱን ለመግለጽ የመለኮታዊውን ስም ተጠቀመበት ከሚለው ድምዳሜ ማምለጥ ይከብዳል። ይህ ደግሞ የግሪክን መጽሐፍ ቅዱስ ለሚያውቅ ማንኛውም የአንደኛ ክፍለ ዘመን አንባቢ ሊስተው የማይችል ነው።” [4]
Scott Brazil የተባለውም ሌላ ሊቅ እንዲህ ይለናል ፦
“ድርብ ጥሪ የሆነው κύριε κύριε የሚለው ቃል ለከፍተኛ ስሜት አጽንዖት ለመስጠት የተደጋገመ ሳይሆን፣ በግሪክ የብሉይ ኪዳን ትርጉም (LXX) ውስጥ ለመለኮታዊው ስም (ለእግዚአብሔር ስም) እንደ ምትክ ያገለግል ነበር።” [5]
በመጨረሻም ለጥቅሱ ሌላ ትርጉም የሰጠው ፣ ራሱንስ ያታለለው ማን ነው? የሚለውን እንድትለዩ ፍርዱን ለአንባቢያን በመተው መጣጥፋን እዚህ ጋር የምቋጭ ይሆናል።
አሜን ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና !
✍ በዲ/ን አናሲሞስ የተጻፈ
https://t.me/ZeathanAmharic🌱🌱🌱🌱🌱🌱🌱🌱🌱🌱🌱
1). ክርስቶስ ማን ነው? 303 ወሳኝ ጥያቄዎች በኡስታዝ አሕመዲን ጀበል ፣ ገጽ 29 - 30
2). ኢሳይያስ 28:16 ፣ ሕዝ 37:21
3). Matthew ; exegetical guide to the greek new testament by Charles L.Quarles ,pp.153
4). ‘Lord, LORD’: Jesus as YHWH in Matthew and Luke by Jason A. Staples
5). Jesus and YHWH - texts in the synoptic gospels by Scott Brazil , pp.101